“የሰላም ብሔራዊ በጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ አገልግሎት በማንነቶች ላይ መሠረት አድርጎ ያለውን መከፋፈልና ጥርጣሬ በማስወገድ የወጣቶችን የሀገርና የሕዝብ ፍቅር ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና እያበረከተ ነው፡፡” ክቡር አቶ ቸሩጌታ ገነነ
Publicador de continguts
“የሰላም ብሔራዊ በጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ አገልግሎት በማንነቶች ላይ መሠረት አድርጎ ያለውን መከፋፈልና ጥርጣሬ በማስወገድ የወጣቶችን የሀገርና የሕዝብ ፍቅር ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና እያበረከተ ነው፡፡” ክቡር አቶ ቸሩጌታ ገነነ
ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም የወጣቶች በጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት ለ9ኛ ዙር በጅማ ዩኒቨርሲቲ ስልጠና የወሰዱ ሰልጣኞች ስልጠናውን በስኬት አጠናቀው ተመርቀዋል፡፡
በስልጠናው የተሳተፉት ከሁሉም የሀገራችን ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተወጣጡ፤ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ወጣቶች ናቸው፡፡ ወጣቶቹ ሀገራችን ሲያጋጥሟት የነበሩትን አፍራሽ አስተሳሰቦች ሰብረው ኢትዮጵያዊ ፍቅርን ተላብሰው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በመስጠት ለሀገራዊ የሰላም ግንባታ እና ብሔራዊ መግባባትን የሰላም አምባሳደርነት ሚና የመወጣት ዓላማ ያነገቡ በጎ ፈቃደኞች ናቸው፡፡
በምረቃው መርሐ ግብር ክቡር አቶ ቸሩጌታ ገነነ በሰላም ሚኒስቴር የፌደራሊዝምና ግጭት አስተዳደር ዘርፍ ሚኒስትር ዴዔታ ተገኝተው ባስተላለፉት መልእክት ዘላቂ ሰላም፤ የዜግነት ክብር እና ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት ዐድጎ የማየት ርዕይን ቀርጾ የዜጋውን፣ የማኅበረሰቡን እና የቤተሰቡን ሰላም በማስጠበቅና በማስከበር፤ ብሔራዊ መግባባትን፣ ሀገራዊ አንድነትን በማሳደግ የፌደራል ሥርዓቱን በማጠናከር፣ ቀጠናዊና አህጉራዊ ትብብርን በማጎልበት አዎንታዊ ሰላምን ለማሰፈን ከሚደረግ ጥረት ቁልፍ ጉዳዮች መካከል የሰላም ብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ ልማት አገልግሎት በዋናነት የሚጠቀስ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጀማል አባፊጣ (ዶ/ር) “የሰላም ብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ ልማት አገልግሎት ፕሮግራም ወጣቱን በአመለካከትና በሥነ-ምግባር እንዲታነጽ ከማድረግ ባሻገር ብቁ ዜጋን ማፍራት የሚያስችል ብሎም በሰላም ግንባታ ሂደት ውስጥ ወጣቶች ሀገራችንን እና ማኅበረሰባችንን እንዲያውቁ፣ እንረዱና የሀገር ፍቅር ስሜት በውስጣቸው እንዲሰርጽ የሚያደርግ ስለሆነ በተሰማሩት መስክ ሁሉ ማኅበረሰብን በእውነትና በዕውቀት በማገልገል ለታዳጊዎችና ለሌሎች ወጣቶች መልካም አርአያ የሚሆኑበት ነው” ብለዋል፡፡
ተመራቂዎቹ የሰላም ብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ ልማት አገልግሎት ተሳታፊዎችም በሚሰማሩባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች ሁሉ የማህበረሰብ ልማት አገልግሎት በመስጠት በሀገር ግንባታው የራሳቸውን አሻራ ለማሳረፍ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡