13ኛ ዙር የብሔራዊ የበጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት ስልጠና በጅግጅጋ ዩኒቨርስቲ የመክፈቻ ፕሮግራም ተካሄደ
Asset-Herausgeber
ግንቦት 17/2017 ዓ.ም (የሰላም ሚኒስቴር)፣ ለ13ኛ ዙር የብሔራዊ የበጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም ለመሰልጠን በጅግጅጋ ዩኒቨርስቲ የገቡ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች የእንኳን ደህና መጣችሁ ፕሮግራም ተካሂዷል።
በስልጠናው የመክፈቻ ፕሮግራም ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት በሰላም ሚኒስቴር የሥራ አመራር ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መብራቱ ካሳ፣ በሚኒስቴር መ/ቤቱ በጎነት ለአብሮነት በሚል መሪ ሃሳብ የተጀመረው የብሔራዊ በጎ ፈቃድ የማህበረሰብ አገልግሎት መርሐ-ግብር ኢትዮጵያዊ እሴቶችንና መርሆችን ለወጣቱ ትውልድ በማስተላለፍ በዘር፣ በጎሳ፣ በሃይማኖት እና በሌሎችም ማንነቶች ላይ መሰረት አድርጎ ያለው ልዩነት ጌጥ እንጂ ዕዳ አለመሆኑን በመገንዘብ፤ በህብረ-ብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ጠንካራ ሀገርን ለመገንባት በተለይ የወጣቶችን የሀገር ፍቅርና የህዝብ ፍቅር ለማሳደግ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል።
አቶ መብራቱ አክለውም፣ የ13ኛው ዙር የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ለየት የሚያደርገው በሰላም በጎ ፈቃድ አገልግሎት ባለፉት 12 ዙሮች ያለው አፈጻጸም ከተገመገመበት ማግስት ሲሆን፤ ፕሮግራሙ የወጣቶች የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ትስስርን ከማጠናከር ባሻገር ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችን ያቃለለ መሆኑን ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። በተጨማሪም በጎ ፈቃደኞች የማህበረሰቡን ችግሮች ከማቃለል ባለፈ ዘላቂ ዝምድናና ለሰላም እሴት ግንባታ መጠናከር ያደረጉትን አስተዋኦ እንደ አብነትም ጠቅሰዋል።
በመጨረሻም የሰላም ሚኒስቴር የሰላም ብሔራዊ በጎ ፈቃድ ማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም በመንደፍ የሀገር ግንባታ መሰረታውያንን ለአዲሱ ትውልድ የማስተላለፍ ስራን ትኩረት ሰጥቶ መስራት ላይ እንደሚገኝ ገልጸው፤ በጎ ፈቃደኞች የሰላም በጎ ፈቃድ የማህበረሰብ ሥራ ላይ መሳተፍ ከእድለኛነት ባሻገር የህሊናና የመንፈስ እርካታ የሚሰጥ ተግባር መሆኑን በመገንዘብ የራሳቸውን አዎንታዊ አሻራ በማሳረፍ የዜግነት ግዴታቸውን እንደሚወጡ እንደሚተመኑ ገልጸው፤ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸውን በጥብቅ ዲሲፕሊን እንዲከታተሉ አሳስበው፤ መልካም የስልጠና ጊዜ እንዲሆንላቸው በመመኘት ንግግራቸውን አጠቃልለዋል።

የጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝዳንት ዶ/ር አብዲ አህመድ በበኩላቸው የበጎ ፈቃድ ሰልጣኞች እንኳን ወደ ትንሿ ኢትዮጵያ ተምሳሌት ወደ ሆነችው ዩኒቨርሲቲያችን በደህና መጣችሁ ብለው፤ ሰልጣኞች በቆይታቸው በዲሲፕሊን እና በሀላፊነት ስሜት እንዲሆን አሳስበዋል።

በመድረኩ ላይ የተገኙት የሱማሊ ክልል የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ም/ሃላፊ አቶ መሀመድ መሀሙድ ባስተላለፉት መልዕክት የብሔራዊ በጎ ፈቃድ የማህበረሰብ አገልግሎት ዓላማ ሳንነጣጠል አብረን የምንሰራው ስራ ነው። በመሆኑም እንደ ክልልም ቀደም ባሉ ዙሮች ተጠቃሚዎች መሆናቸውንና ከሀገራዊ ፋይዳው አንጻር ቤተሰባዊነትን እንድንመሰርት እድል የፈጠረ ፕሮግራም ነው ብለዋል።
የመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ላይ የጅግጂጋ ከተማ አስተዳደር የከንቲባው ተወካይ፣.የሀገር ሽማግሌዎች፣ የክልሉ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ም/ሃላፊ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና ሰራተኞች በተገኙበት በሀገር ሽማግሌ ምርቃት የተከፈተ ሲሆን፤በብሔር ብሔረሰቦች ዝማሬና ትዕይንት ደምቆ ተካሂዷል።
የሰላም ሚኒስቴር ከ2013 ዓ.ም ጀምሮ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችን በብሔራዊ በጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ አገልግሎት በማሳተፍ በሥነ ምግባር፣ በክሕሎት እና በሥራ ፈጠራ ግንዛቤ የሚያዳብር ስልጠናዎችን በመስጠት ወደ ተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች እየተሰማሩ የተለያዩ ማኅበረሰባዊ አገልግሎቶችን እየሰጡ እንደሚገኙ ይታዎቃል።